አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 19፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በአትላንቲክ ምክር ቤቱ የአፍሪካ ማዕከል ባልደረባ የሆኑት ብሮንዋይን ብሩተን እና የባልሲሊዓለማቀፋዊ ጉዳዮች ትምህርት ቤት ሊቀ-መንበር እንዲሁም የዓለም አቀፍ ደኅንነት ፕሮፌሰር አን ፊትዝ-ጀራልድ ፎሬይን ፖሊሲ መፅሄት ላይ ባወጡት ፅሑፍ፥ ምንም እንኳን አሜሪካ ለአሸባሪ ቡድኑ ህወሃት በማድላት ሥህተት ሥትፈጽም ብትቆይም አሁንም ለሰሜን ኢትዮጵያ ግጭት ማብቃት አወንታዊ ሚና ለመጫወት ያላት ዕድል አልተሟጠጠም ሲሉ ገልጸዋል፡፡
ምሁራኑ በጽሑፋቸው ከአራት ዓመት በፊት ለ27 ዓመታት ሲገዛ በነበረው አንባገነኑ የህወሓት ቡድን ላይ ህዝባዊ አመጽ እንደተቀሰቀሰና አገዛዙ እንደተገረሰሰ አስታውሰዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ወደ ማዕከላዊ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ምንም እንኳን በህወሓት ታፍነው የቆዩ የብሄር ጥያቄዎች እየፈነዱ ሀገሪቷ ባትረጋጋም በርካታ ማሻሻያዎች አድርገው የዜጎችን ጥያቄዎች በልካቸው ለመመለስ እንደሰሩ ጽፈዋል፡፡
ነገር ግን ይላሉ ጸሐፊዎቹ ምንም እንኳን አሸባሪ ቡድኑ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን መንግስት አልቀበልም ብሎ በማመጽ ወደ ትግራይ ሄዶ ቢመሽግም ቡድኑ ቀደም ብሎ በዘረጋው የእንደራሴዎቹ ሠንሠለት የሀገሪቷን ኢኮኖሚ እና የመከላከያ ኃይል መልሶ ለመቆጣጠር ሰርቷል ብለዋል፡፡
የውክልና ሥራውን ለማስፈጸምም ከሀገሪቷ የዘረፈውን በቢሊየን ዶላሮች የሚቆጠር ሐብት ጥቅም ላይ እንዳዋለ አንስተዋል፡፡
በወቅቱ አብዛኞቹ ምዕራባውያን በለውጡ ሲደሰቱ አንዳንዶቹ ግን ከህወሓት ጋር ወታደራዊ ግጭት ሊፈጠር እንደሚችል ሲናገሩ እንደነበርም ጽሁፉ ያወሳል፡፡
ጸሐፊዎቹ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከኤርትራ ጋር ሠላም መፍጠሩ ለኖቤል የሠላም ሽልማት እንዳበቃቸው፣ በሀገራቱ መካከል ለሁለት አሥርት ዓመታት አኮራርፏቸው የዘለቀው የድንበር ጉዳይም በዕርቁ መፈታቱ ህወሓትን እንዳስኮረፈውና ጥግ እንዳስያዘው፣ ህወሓት በኤርትራ ድንበር አቅራቢያ ያሰፈራቸውን ኃይሎች ትጥቅ እንዲያስፈታ መንግስት ቢጠይቅም አሻፈረኝ እንዳለ፣ ይህም ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ራስ ምታት ሆኖ መቆየቱን ዘርዝረዋል፡፡
ጽሑፉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ሠላምን ለማስፈንና ዕርቅ ለመፍጠር በርካታ የዕርቀ-ሠላም ልዑካን ወደ ትግራይ ቢልኩም በአሸባሪው የህወሓት ቡድን እብሪት እንዳልተሳካ አመላክቷል፡፡
ጸሐፊዎቹ፥ ዐቢይ አህመድ በርካታ የህወሓትን ባለሥልጣናት ማንሳቱ፣ በተለይም የወታደራዊውን ማዕከላዊ ዕዝ በፈለጋቸው አመራሮች መተካቱ እና በትግራይ ተወላጆች ቁጥጥር ሥር ብቻ የነበረው የዕዝ ሠንሠለት በበርካታ ብሄሮች ስብጥር መተካቱ እንዳስደነገጣቸው፣ እንዳስኮረፋቸው እና ወደ ጦርነት ለመግባት መስማማት ላይ እንዳደረሳቸው ገልጸዋል፡፡
የትግራይ ባለሥልጣናት በሰሜን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ዕዝ ላይ የፈጸሙት “መብረቃዊ ጥቃት” ጦርነትን ቋቅሷል ብለዋል፡፡
አሸባሪው የህወሓት ቡድን ከዚህ ጥቃት በኋላ የአማራን ዘር ለማጥፋት በሚመስል መልኩ በማይካድራ በበርካታ መቶዎች የሚቆጠሩ አማራዎችን መጨፍጨፉን አስታውሰዋል፡፡
የምዕራባውያኑ መገናኛ ብዙኃንም ጭፍጨፋውን በማነሳሳቱ ረገድ መንግስት ተጠያቂ መሆን እንዳለበት እንዲሁም በትግራይ ላይ የዘር ማጥፋት እንደፈጸመ አድርገው አጀንዳ በመቅረጽ መሥራት መጀመራቸውን ብሮንዋይን ብሩተን እና አን ፊትዝ-ጀራልድ በጋራ ባወጡት ጽሑፍ አመልክተዋል፡፡
መገናኛ ብዙኃኑ ከህወሓት ባልተናነሰ ለአሸባሪው ሸኔም እውቅና በመስጠት ከተገፋው ህወሓት ጋር በማበር የኦሮሞን ህዝብ ከጭቆና ነጻ ለማውጣት በጋር እየሠሩ መሆናቸውን ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ለማሳመን ሲሰሩ ቆይተዋልም ይላል ጽሑፉ፡፡
ከመገናኛ ብዙኃኑ በተጨማሪ ዓለምአቀፍ የዕርዳታ ድርጅቶችም ህወሓትን ሲደግፉ መቆየታቸው ተመላክቷል፡፡
አሁን አሁን አሸባሪው የህወሓት ቡድን እየተዳከመ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ መገናኛ ብዙኃኑ ጉዳዩን እንደ ቀድሞው ከማራገብ ጋብ ብሏልም ይላሉ – ጸሐፊዎቹ፡፡
ፀሃፊዎቹ የፕሬዚዳንት ጆ ባይደን አስተዳደር ያለምንም ምክንያት የአሸባሪ ቡድኑን ህወሃት ወንጀል ለመሸፈን በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ብቻ ያነጣጠረ ቅጣት እየጣለ መቆየቱን አንስተዋል።
ምንም እንኳ ጦርነቱን የቀሰቀሰው፣ ከሰሜን እዝ የጦር መሳሪያን ዘርፎ እና ቁጥሩ አያሌ የሆነ ሚሊሻ ያሰለፈው ህወሃት ሆኖ ሳለ የምእራቡ ዓለም መገናኛ ብዙሃን የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ መንግስትን የጦርነት ቀስቃሽና ፈላጊ አድርገው መሳላቸውን ነው ያመለከቱት።
በዚህ መልኩ ዩናይትድ ስቴትስ ለህወሃት በማድላት ለአሸባሪ ቡድኑ የፖለቲካ ድጋፍ መስጠቷን በመጠቆም ስህተት መፈፀሟን አመልክተዋል። የባይደን አስተዳደር ይህንን የተሳሳተ አካሄዱን በማረም የሰሜን ኢትዮጵያን ግጭት በማቆሙ አወንታዊ ሚና ለመጫወት አሁንም እድል እንዳለው መክረዋል።
ህወሃት ከአማራ እና አፋር ክልሎች ተሸንፎ መውጣቱን የሚያነሱት ፀሃፊዎቹ፥ ይህ ቡድን በተተኳሽ እጦት እና በሎጀስቲክ ድርቅ ምክንያት ምንም ወታደራዊ ስኬት የማየት እድል የለውም ባይ ናቸው።
እናም ዩናይትድ ስቴትስ ቁልፍ የህወሃት አመራሮች እጃቸውን እንዲሰጡ በይፋ በመጠየቅ፥ ለዚህ የሽብር ቡድን ምንም ድጋፍ እንደሌላት ለኢትዮጵያ ህዝብ ልታሳይ ይግባል ይላሉ።
እነዚህ ቁልፍ የህወሃት አመራሮች ሰላምን በመምረጥ እጅ ለመስጠት ፈቃደኛ ካልሆኑም በውጭ ዓለም የተከማቸ ሀብት እና ቤተሰብ ባላቸው በእነዚህ የህወሃት መሪዎች ላይ ማእቀብ ልትጥል እንደሚገባ ገልፀዋል።
አሜሪካ አጀንዳዎቿን የሚያስፈጽሙ መገናኛ ብዙኃን፣ የእርዳታ ድርጅቶች በሰብዓዊነት ስም የሚንቀሳቀሱ ካውንስሎች እና ኤጀንሲዎች፣ ተጽዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦቿን ጋብ እንዲሉ በማድረግ እና አሸባሪው ቡድን ለፈፀማቸው ጥሰቶች ሁሉ በወንጀል ተጠያቂ የሚሆንበትን ምህዳር በማመቻቸት በኢትዮጵያ ላይ የፈጸመችውን አድልዖ እና በደል በመጠኑም ቢሆን መካስ እና ግንኙነቷን ወደ ቀደመው ሁኔታ መመለስ እንደምትችል ምሁራኑ ባሰፈሩት ጽሑፍ መክረዋል፡፡