የሀገር ውስጥ ዜና

ፈተናዎችን በመሻገር ጠንካራ ሀገር ለመገንባት የዓድዋ ድልን መጠቀም አለብን – አይሻ መሀመድ (ኢ/ር)

By Feven Bishaw

March 02, 2025

አዲስ አበባ፣ የካቲት 23፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ያጋጠሙንን ፈተናዎች በመሻገር ጠንካራና የበለጸገች ሀገር ለመገንባት የዓድዋ ድልን መጠቀም እንደሚገባ የመከላከያ ሚኒስትር አይሻ መሀመድ (ኢ/ር) ገለጹ፡፡

129ኛው የዓድዋ ድል በዓል “ዓድዋ የጥቁር ሕዝቦች ድል” በሚል መሪ ቃል በዓድዋ መታሰቢያ በተለያዩ ሁነቶች እየተከበረ ይገኛል።

የመከላከያ ሚኒስትር አይሻ መሀመድ (ኢ/ር) በበዓሉ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት÷ አንድነታችንን በማጠናከርና የገጠሙንን ፈተናዎች በመሻገር ጠንካራና የበለፀገች ኢትዮጵያና አፍሪካን ለመገንባት መጠቀም ይገባል ብለዋል።

ዓድዋ የምንዘክረው ታሪክ ብቻ ሳይሆን ለትውልድ የምናወርሰው ታላቅ ሃላፊነት ነው ያሉት ሚኒስትሯ÷ ዓድዋ አፍሪካዊያን ለነፃነት የሚያደርጉትን ንቅናቄ በማቀጣጠል ለድል እንዳበቃቸው ገልጸዋል፡፡

ዛሬም በህብረትና በጀግንነት በመነሳሳት ለሀገራችንና ለአፍሪካ ብልፅግና ለማረጋገጥ መትጋት እንደሚገባ ማሳሰባቸውን ከመከላከያ ሰራዊት ማኅበራዊ ትስስር ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡