አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 7፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ከግለሰብ አስፈራርተው ጥፍጥፍ ወርቅ ወስደዋል የተባሉ ተከሳሾች እስከ 20 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ተቀጡ።
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የሙስና ጉዳዮች ወንጀል ችሎት የግራ ቀኝ ሚስረጃ መርምሮ የቅጣት ውሳኔውን አሳልፏል።
የቅጣት ውሳኔ የተወሰነባቸው ተከሳሾቹ÷ 1ኛ ተከሳሽ የቀድሞ የአዲስ አበባ ከተማ የሰላም እና ፀጥታ ዘርፍ አባልና የቀድሞ ወታደር የነበረው ሻለቃ ፀጋዬ ሀይሉ፣ 2ኛ ደበበ ገመዳ፣ 3ኛ ሰናይት ብርሃኑ እና 4ኛ አለማየሁ ደነቀ ናቸው።
የፍትህ ሚኒስቴር የሙስና ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዐቃቢ ህግ በ2015 ዓ.ም መጨረሻ በተከሳሾቹ ባቀረበው ዝርዝር ክስ ላይ እንደተመላከተው ተከሳሾቹ በየካቲት 21 ቀን 2015 ዓ.ም የግል ተበዳይ ከትግራይ ይዞት የመጣውን 1 ሺህ 611 ግራም ጥፍጥፍ ወርቅን ለማሰራት ወደ ፒያሳ ከ3ኛ ተከሳሽ ጋር አብረው ሲጓዙ ወርቁን እንዲወስዱበት ለማድረግ 3ኛ ተከሳሽ ከ1ኛ፣ 2ኛ እና 4ኛ ተከሳሾች ጋር መስማማቷ ተጠቅሷል።
በስምምነታቸው መሰረት 3ኛ ተከሳሽ ቃተና ተብሎ ወደ ሚጠራ ምግብ ቤት ምሳ እንብላ በማለት የግል ተበዳይን ወደ ምግብ ቤቱ በመውሰድ ምግብ ቤት እንደደረሱ 1ኛ ተከሳሽ የወታደር ልብስ በመልበስ ራሱን ወታደርና የፀጥታ አካል አስመስሎ የግል ተበዳይ ወደነበረበት ተሽከርካሪ በመቅረብ ተበዳይ ተቀምጦበት ወደ ነበረው የሹፌር ወንበር እንዲወርድና ከኋላ እንዲቀመጥ ካደረገው በኋላ ራሱ ተከሳሹ ወደ መኪናው ገብቶ ጋቢና ከተቀመጠ በኋላ መኪናው በህገወጥ መንገድ ሀገር ውስጥ የገባ ነው በማለትና መኪናውን በጂፒኤስ እየተከታተሉት መሆኑን በመግለጽ፤ መኪናው ይታሰራል በማለት እንዳስፈራራው በክሱ ዝርዝር ላይ ተጠቅሷል።
2ኛ ተከሳሽ ደግሞ የመኪናው የኋላ ወንበር ላይ ገብቶ በመቀመጥና ሽጉጥ አውጥቶ የግል ተበዳይ ጭንቅላት ላይ በመደቀን የግል ተበዳዩ ይዞት የነበረውን 10 ሚሊየን ብር የሚገመት 1 ሺህ 611 ግራም ጥፍጥፍ ወርቅ ነጥቆ መውሰዱ በክሱ ተመላክቷል።
ወርቁን ከነጠቁት በኋላ ተበዳዩን ከመኪናው በማስወረድ በ3ኛ ተከሳሽ አሽከርካሪነት ጥፍጥፍ ወርቁን ይዘው በርቀት ሆኖ ሲጠብቃቸው ከነበረ ከ4ኛ ተከሳሽ ጋር በመሆን ወርቁን ፒያሳ አካባቢ በመውሰድ ህጋዊ ንግድ ፍቃድ ለሌለው ነጋዴ በ3 ሚሊየን 415 ሺህ በመሸጥ እና ገንዘቡን በተለያየ መጠን በመከፋፈል ለግል ጥቅም አውለዋል በማለት ዐቃቢ ህግ ክስ አቅርቦባቸዋል።
በዚህ መልኩ የቀረበባቸውን ክስ ዝርዝር ተከሳሾች በወቅቱ መደበኛ ችሎት ዝግ ስለነበር በተረኛ ችሎት ቀርበው ክሱ ከደረሳቸው በኋላ የክስ ዝርዝሩ በችሎት በንባብ ተሰምቶ ነበር።
ከዚህም በኋላ ተከሳሾች በክሱ ላይ የተጠቀሰውን የወንጀል ድርጊቱን አለመፈጸማቸውን ጠቅሰው÷ የሰጡትን የዕምነት ክህደት ቃል ተከትሎ ዐቃቢ ህግ የግል ተበዳይን ጨምሮ ምስክሮችን አቅርብ አሰምቶ ነበር።
ፍርድ ቤቱ የዐቃቢ ህግ ማስረጃን መርምሮ ተከሳሾቹ እንዲከላከሉ ብይን የሰጠ ቢሆንም፤ ተከሳሾች የዐቃቢ ህግ ማስረጃን ማስተባበል አለመቻላቸው ተጠቅሶ የጥፋተኝነት ፍርድ ተሰጥቶባቸዋል።
በዚህም በተለይም 1ኛ፣ 2ኛ እና 3ኛ ተከሳሾች በ1ኛ ክስ ማለትም በወንጀል ህግ አንቀጽ 670 በወንብድና ወንጀል እና በ2ኛ ክስ በወንጀል የተገኘ ገንዘብ ወይም ንብረት ህጋዊ አስመስሎ ማቅረብ ማለትም በአዋጅ ቁጥር 780/2005 አንቀጸሰ 29 ንዑስ ቁጥር 1 ስር ጥፋተኛ የተባሉ ሲሆን፣
4ኛ ተከሳሽ ግን በ2ኛ ክስ ብቻ በአዋጅ ቁጥር 780/2005 አንቀጽ 29 ንዑስ (1) ስር በወንጀል የተገኘ ገንዘብ ወይም ንብረት ህጋዊ አስመስሎ በማቅረብ ጥፋተኛ ተብሏል።
ከዚህም በኋላ ፍርድ ቤቱ አጠቃላይ የግራ ቀኝ የቅጣት አስተያየት በመመርመርና በመያዝ ዛሬ ከሰዓት በኋላ በነበረ ቀጠሮ÷ 1ኛ፣ 2ኛ እና 3ኛ ተከሳሾችን እያንዳንዳቸው በ20 ዓመት ፅኑ እስራት እና በ30 ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጡ ወስኗል፡፡
4ኛ ተከሳሽን ደግሞ በ2ኛ ክስ ብቻ በ6 ዓመት ፅኑ እስራት እና በ3 ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጣ ወስኗል።
በታሪክ አዱኛ