በሽረ እንዳስላሴ በቀዳማዊት እመቤት ጽ/ቤት ድጋፍ እየተገነባ ያለው ት/ቤት በቀጣዩ ዓመት ይጠናቀቃል
አዲስ አበባ፣ የካቲት 13፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በትግራይ ክልል ሽረ እንዳስላሴ ከተማ በቀዳማዊት እመቤት ጽሕፈት ቤት ድጋፍ እየተገነባ የሚገኘው 2ኛ ደረጃ ት/ቤት በቀጣዩ ዓመት ተጠናቅቆ አገልግሎት እንደሚሰጥ ተገልጿል፡፡
የከተማው የትምህርት ቤቶች ጽ/ቤት ኃላፊ ገብረመድህን ወልደ ጊዮርጊስ እንዳሉት ÷ ትምህርት ቤቱ እየተገነባ የሚገኘው የቀዳማዊት እመቤት ጽሕፈት ቤት በሰጠው የ20 ሚሊየን ብር ድጋፍ ነው።
ግንባታው በጥራትና በፍጥነት እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው÷ በቀጣዩ ዓመት ተጠናቅቆ አገልግሎት እንደሚሰጥ ጠቁመዋል።
የትምህርት ቤቱ ግንባታ ሲጠናቀቅም በሁለት ፈረቃ 1 ሺህ 600 ተማሪዎችን ተቀብሎ የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
ትምህርት ቤቱ ቤተ-ሙከራዎችና ቤተ መጽሐፍት እንዲሁም ለአስተዳደር እና ሌሎች አገልግሎቶች የሚውሉ ክፍሎችን ያካተተ ነው ተብሏል፡፡