Fana: At a Speed of Life!

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) የዒድ አል-ፈጥር በዓልን አስመልክቶ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 20፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) 1 ሺህ 446ኛው የዒድ አል-ፈጥር በዓልን አስመልክቶ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ።

የጠቅላይ ሚኒስትሩ መልዕክት ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል:-

እንኳን ለ1446ኛው የዒድ አል ፈጥር በዓል አደረሳችሁ፡፡

“ዒድ አል ፈጥር” የረመዳን ጾምን የማጠናቀቂያ በዓል ነው፡፡ ዒድ አል ፈጥር “የምስጋና፣ የበጎ አድራጎት እና የወንድማማችነት/እኅትማማችነት” በዓል ነው፡፡ ዒድ አል ፈጥር ከአንድ ወር የጾም ጊዜ በኋላ የሚመጣ በዓል ነው፡፡ ጾሙ የሰውን ድካም፣ ዐቅም ማነስ እና ልክ የሚያሳይ ነው፡፡ ፈጣሪ ካልደገፈው በቀር የሰው ልጅ ዐቅም ውሱን መሆኑን ያሳያል፡፡ ትዕቢት፣ ጥጋብ እና ክፋት በዚህ ደካማ ሰው ላይ መብቀላቸውን ለተመለከተ፣ የሰው ጠላቱ የገዛ ጠባዩ መሆኑን ይማራል፡፡ ሰው በዘመናት ውስጥ ሌሎችን ለመግዛት የታገለውን ያህል ራሱን ለመግዛት አልታገለም፡፡ ዛሬም በሀገራችን የምናየው ፈተና በዋናነት ራስን ካለመግዛት የሚመጣ ፈተና ነው፡፡ ራሱን የማይገዛ ሰው ዐቅሙን አያውቀውም፡፡ ወደ ውስጡ አያይም፡፡ ጠላቱን ከገዛ ጠባዩ ውስጥ ከመፈለግ ይልቅ፣ ጠላቱን ከጎረቤቱ ይፈልገዋል፡፡ በዚህ የተነሣ ከገዛ ወገኑ ጋር ሲቃረን ይኖራል፡፡ እንደ ረመዳን ዓይነት ወቅቶች ውስጥን ለመመልከት የሚጠቅሙ ናቸው፡፡

ውስጣቸውን የተመለከቱ ሰዎች ምስጋና ገንዘባቸው ነው፡፡ ሰው የራሱን ልክ ካላወቀ ሌላውን አያደንቅም፤ ሌላውን አያመሰግንም፡፡ የሌለውን ካልተረዳ ያለውን አያውቅም፤ አያደንቅም፡፡ የራሱ ጠላት የገዛ ጠባዩ መሆኑ ካልገባው፣ ሌላውን ወገኑን አያፈቅርም፡፡ ለዚህ ነው የጾሙ መጨረሻ፣ ዒድ አል ፈጥር የምስጋና በዓል የሆነው፡፡ ጾሙ ከቤተሰብ ጀምሮ እስከ ማኅበረሰብ ድረስ ራስን ገዝቶ ለመሰባሰብ ይጠቅማል፡፡ መሰባሰቡም ከስሜት የወጣ፣ ስክነትና ራስን መግዛት ያለበት ነው፡፡ ሀገራዊ ምክክራችን ይሄን ዕሴት ቢላበስ እንጠቀማለን፡፡ መነጋገሩ ብቻ አይጠቅምም፡፡ ከስሜት ወርዶ፤ በስክነት ተሞርዶ፤ ነገን ተመልክቶ – መመካከር፡፡ ያ ከሆነ እንደ ዒድ ሁሉ፣ የምክክራችን ፍጻሜው ምስጋና ይሆናል፡፡

የዒድ ሌላው ዕሴት በጎ አድራጎት ነው፡፡ ዐቅም ለሌላቸው፤ ሁኔታው ላልተሟላላቸው ወገኖች መልካምን ነገር ማድረግ፡፡ ዝምድናን፣ ዘርን ወይም እምነትን ሳይመለከቱ ሰውን በሰውነቱ ብቻ መርዳት፡፡ የጾም ምንዳዕ ሙሉ የሚሆነው በጎ አድራጎት ከተጨመረበት ነው፡፡ በጎ አድራጎት ማለት ከራስ አጉድሎ ሌላውን መሙላት ነው፡፡ እንደ ሀገር ለመቀጠልና እንደ ሕዝብ ለመተሣሠር በጎ አድራጎት እጅግ አስፈላጊ ዕሴት ነው፡፡ ራስን በሌላው ጫማ ላይ አስገብቶ ማየት፡፡ የሌላው ጉድለት ለመሙላት ሲባል የራስን ማጣት፡፡ ለምን ወገኔ ያዝናል? ለምን ወገኔ ይከፋል? ብሎ መንገብገብ፡፡

ሁላችንም የየራሳችንን ወገን ጥቅምና መብት በማስከበር ብቻ ሀገር ልንገነባ አንችልም፡፡ ትሥሥራችን ወገን ዘለል ሆኖ፣ የሌላውን ወገን ጉዳትና ፈተና መጋራት ይገባናል እንጂ፡፡ የእኔ ቤት ሲሟላ አይደለም የእርሱ ቤት የሚሟላው፡፡ የእርሱ ቤት ሲሟላ ነው የእኔ ቤት የሚሟላው፡፡ የፖለቲካ ምኅዳራችን በዚህ ነባር ዕሴታችን ላይ ካልተመሠረተ ፍትሐዊነትን እና እኩልነትን ለማስፈን እንቸገራለን፡፡

እነዚህን ሁለቱን ዕሴቶች የሚያስተሣሥረው የዒድ ዕሴት “ወንድማማችነት/እኅትማማችነት” ነው፡፡ ወንድማማችነት/ እኅትማማችነት ማለት በጋራ ዕሴቶች፣ በመተባበር እና በጋራ ግብ ላይ የተመሠረተ ወዳጅነት ነው፡፡ ይሄ ወዳጅነት በሥነ ምግባር የተገራ፣ ፍቅርንና አንዱ ለሌላው መቆምን መሠረት ያደርጋል፡፡ የጋራ ኃላፊነትን ይወስዳል፡፡ በሀገራችን የፖለቲካ ሕይወት እጅግ አስፈላጊው/ግን እጅግ የተረሳው ዕሴት ነው፡፡ መብትንም ሆነ ግዴታን በወንድማማችነት/እኅትማማችነት መነጽር መመልከት ነገሩን ለሰውነት ቅርብ ያደርገዋል፡፡ ለእኔ ከሚለው አውጥቶ ለእኛ፤ ለእኛ ከሚለውም ጭምር አውጥቶ “ለእነርሱ እና ለእኛ”፤ ለእነርሱ እና ለእኛ ከሚለውም አውጦቶ “ለእኛ ይቅርብን፤ ለእነርሱ ይደረግ “ወደሚለው የላቀ ሰብእና ያደርሰዋል፡፡

በእምነቶች፣ በፖለቲካ ፓርቲዎች፣ በማኅበረሰቦች እና በልሂቃን መካከል የተሻለውን አብሮነት የሚፈጠረው ወንድማማችነት/እኅትማማችነት ነው፡፡ የተሻለ መረዳዳት፣ የተሻለ መተዋወቅ እና የተሻለ መግባባት ይፈጥራል፡፡ ለሌላው ሲል መተዉን፤ ለሌላው ሲል መቀበልን እና ለሌላው ሲል ለበደሎች ዕውቅና መስጠትን የሚያስገኘው ዕሴት – ወንድማማችነት/እኅትማማችነት ነው፡፡ የዒድ በዓል አንዱ ዕሴት የሆነውም በዚህ የተነሣ ነው፡፡ የዒድን በዓል እነዚህን የበዓሉ ዕሴቶች እያሰብን፣ እያዳበርንና ለሀገር ግንባታ እየተጠቀም እንድናከበረው ጥሪ አቀርባለሁ፡፡ ቤተሰቦች፣ ጎረቤታሞች፣ ማኅበረሰቦች እና የእምነት አባቶች ሲሰባሰቡ እነዚህ ሦስት የዒድ ዕሴቶች ጎልተው እንዲወጡና ማኅበረሰባችን እንዲገነባባቸው እንዲያደርጉ አደራ እላለሁ፡፡

ኢድ ሙባረክ!
ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!
ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ!
መጋቢት 20፣ 2017 ዓ.ም

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.