Fana: At a Speed of Life!

በኢ ቢ ኤስ ቴሌቪዥን ‘አዲስ ምዕራፍ” ፕሮግራም ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ ተወሰደ

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 23፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን በኢ ቢ ኤስ ቴሌቪዥን ጣቢያ ‘አዲስ ምዕራፍ’ በተሰኘ ፕሮግራም ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መውሰዱን አስታወቀ።

ባለስልጣኑ ፕሮግራሙ እሑድ መጋቢት 14 ቀን 2017 ዓ.ም ያሰራጨውን ፕሮግራም ከመገናኛ ብዙኃን አዋጅ እና ከዘርፉ ሕጎች አንጻር መገምገሙን ገልጿል።

በዚሁ መሰረት በጣቢያው የቀረበው ፕሮግራም በሐሰተኛ መረጃ ላይ የተመሰረተ፣ ሕዝብን የሚያሳስትና ጥርጣሬን የሚፈጥር፣ የመገናኛ ብዘኃን አዋጅ 1238/2013፣ የጥላቻ ንግግርና ሐሰተኛ መረጃ ስርጭትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በወጣው አዋጅ 1185/2012 እንዲሁም የጋዜጠኝነት ሙያ ስነ-ምግባርን፣ መደበኛ የጋዜጠኝነት አሰራርን የሚጥስ የፓራጆርናሊዝም አሰራርን የተከተለ ሆኖ ተገኝቷል ብሏል፡፡

ጣቢያውም በፕሮግራሙ ዙሪያ ተጠይቆ ለባለሥልጣኑ በሰጠው ምላሽ ያሰራጨው ፕሮግራም ሐሰተኛ መሆኑንና ስህተት መፈጸሙን ማረጋገጡን ባለሥልጣኑ ባወጣው መረጃ አመላክቷል።

ባለሥልጣኑ ጉዳዩን መርምሮ በጣቢያው የሚሰራጨው “አዲስ ምዕራፍ” የተሰኘ ፕሮግራም በኤዲቶሪያል አሰራሩ ላይ አስፈላጊውን እርምት ወስዶ ለባለሥልጣኑ እስኪያሳውቅና ውሳኔ እስኪያገኝ ድረስ ፕሮግራሙ ከስርጭት ታግዶ እንዲቆይ መወሰኑን እና የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ የተሰጠ መሆኑን ገልጿል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.