ማንቼስተር ሲቲ ኤቨርተንን አሸነፈ
አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 11፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በ33ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ ማንቼስተር ሲቲ ከሜዳው ውጪ ተጉዞ ኤቨርተንን 2 ለ 0 በሆነ ውጤት አሸንፏል፡፡
የማንቼስተር ሲቲን የማሸነፊያ ግቦች ኦ-ሬልይ እና ኮቫቺች ማስቆጠር ችለዋል፡፡
ውጤቱን ተከትሎ ማንቼስተር ሲቲ በ58 ነጥብ 4ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ፤ ኤቨርተን በ38 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡
በሌላ የጨዋታ መርሐ-ግብር፤ ብሬንትፎርድ በሜዳው ብራይተንን አስተናግዶ 4 ለ 2 በሆነ ውጤት አሸንፏል፡፡
የብሬንትፎርድን የማሸነፊያ ግቦች ምቤሞ (2) ዊሳ እና ኖርጋርድ ሲያስቆጥሩ፤ ለብራይተን ደግሞ ዳኒ ዌልቤክ እና ሚቶማ ከመረብ አሳርፈዋል፡፡
ዌስትሀም ዩናይትድ በሜዳው አስቀድሞ መውረዱን ካረጋገጠው ሳውዝሃምፕተን ጋር ያደረገውን ጨዋታ 1 ለ 1 በሆነ አቻ ውጤት ሲያጠናቅቅ፤ ክሪስታል ፓላስ እና ቦርንመዝ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ 0 ለ 0 ተጠናቅቋል፡፡
የሊጉ ጨዋታ ምሽት 1 ሠዓት ከ30 ሲቀጥል አስቶን ቪላ ከኒውካስል ዩናይትድ በቪላ ፓርክ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል፡፡